HOME FOR SPIRITUAL MESSAGE BY FR ZEMENE DESTA

የነፍሴ እረኛ

በልጅነቱ ገና በእምቡልቃ
አድጎ ተመድጎ ሳያበቃ
ክንዱ ሳይጠነክር ጉልበቱ ሳይጠረቃ
የቀለም አባቱን አጅቦ የኔታን ተከትሎ
አጎዛ ለብሶ ደበሎ ኮፌዳውን አንጠልጥሎ
በይ ደህና ሁኝ እናቴ
ለቤተ ክርስቲያኔ ለሃይማኖቴ
ዙሬ ተምሬ በሰው ሀገር እናንተን ላገለግል በእውቀቴ
ይኸው መሄዴ ነው ትምህርት ቤት መውጣቴ ነው ከቤቴ
ብሎ ተሰናብቶኝ ሲወጣ
አካሌ ቅድድ አለ ነፍሴ በአናቴ ወጣ
አልመሰለኝም ነበር ተመለሶ የሚመጣ

ከዚያች ዕለትና ከዚያች ሰዓት ጀምሮ
አእምሮየ በሐሳብ ተወጥሮ
ልቤ ከእሱ ጋር እንደ ዞረ ዓይኔ እንቅልፍ አጥቶ ስጨነቅ
ሞቷል ከእንግዲህ ብየ መርዶየን ስጠባበቅ

አንድ ተማሪ አየሁ አንድ ቀን
ራሱን ጠምጥሞ በሻሽ ቆሞ ሲለመን ከደጄ
እኔም ልዘከር ስወጣ እንጀራ ይዠ በቀኝ እጄ
እንጀራውን ተቀብሎ እንባና ሳቅ ተናነቀው
እኔም ግራ ግብት አለኝ
እንዴት አባቴ ልሁን እንዴት አድርጌስ ልወቀው
ልክ በሰባት ዓመቱ
ለካስ ልጀ ነው እሱ አድጎ ተመድጎ አንደ አባቱ

እኔ እኮ ነኝ እማየ ብሎ ሲስመኝ ጉልበቴን
ድንጋጤው ከልቤ ገብቶ አብረከረከው ሰውነቴን
ፍዝዝ ብየ ለደቂቃ ትንሽ ቆየሁና ቆሜ
በግንባሬ ተደፍቸ መሬቱን ዝቅ ብየ ስሜ
እልልልል…አልኩኝ ድንገት አንገቱ ላይ ተጠምጥሜ

ዓይን ለዓይን እየተያየን
ከበሩ ቆመን ለሁለት ስንላቀስ ብዙ ቆየን
ከዚያም ተያይዘን ወደ ቤታችን ገባን
ሁለታችንም እያነባን
ቁጭ እንዳልን ትንሽ ቆይተን
መጨዋወት ስንጀምር ተረጋግተን

ራሱን በእጁ ደገፍ አርጎ አንገቱን ወደ ቀኝ አዘንብሎ
አሳዛኝ ሕይወቱን ነገረኝ አጫወተኝ እንዲህ ብሎ
ምንም ትንሽ ልጅ ብሆን ለጋ ሰውነቴ ያልበረታ
ለተቀደሰ ዓላማ አሰልፎ ሁሉን አስቻለኝ ጌታ

የቆሎ ትምህርት መማር እየቆረጠሙ ቆሎ
ጎጆ ቀልሶ መኖር ቡቲቶ ለብሶ ደበሎ
የሻገተ እንጀራ እየበሉ ብስል ከጥሬ ቀላቅሎ
እየባነኑ ማደር እንቅልፍ አጥቶ በየዕለቱ
የወገን የሰፈር ትዝታው የቤተሰብ ናፍቆቱ
ከውሻ ጋር መታገሉ ሰፈር ለሰፈር መንከራተቱ
ለቁራሽ እንጀራ ቆሞ በሰው ዓይን መገመቱ
ስንቱ ተወርቶ እማየ እረ ስንቱ እረ ስንቱ

አንዲህ እያለ ልጄ ታሪኩን ሲነገረኝ በጽሞና
ከአባቱ ቤት ሁሉ ተርፎ ሰባት ዓመት በልመና
ያሳለፈውን ሕይወት ስሰማ የገጠመውንም ፈተና
ሆዴ አልችል አለኝና እንባየ መጣኝ እንደገና

አስተዳደጉን እያስታወስኩ ምንም ቢከፋው ሆዴን
የነፍሴ እረኛ ሆነ ልጄ ሊያስተካክልልኝ መንገዴን
ቀሰሰና በሥርዓቱ አብረን መኖር ጀመርን
እያመሰገንን እግዚአብሔርን
ከፍ ያለ ማዕርግ ሲሰጠው
ለቅስና ሲበቃ መልካም ነገር አዩ ዓይኖቸ  
እኔም አንቱ አልኩት ልጀን አንተ ማለቱን ትቸ
በጣም ደስ አለው ልቤን ኮራሁ በልጄ እኔ እናቱ
በአገልግሎት ላይ ተሰማራ ረካች ነፍሴ በትምህርቱ

ነገር ግን መቸ ይሆን እፎይ የሚለው እሱ
ዛሬም አልወረደም ገና የመከራው ቀንበር ከራሱ
ያ ሁሉ ደጅ ጥናት እግርን በውሻ መበላቱ
ለመነቀፍ ለመዋረድ ለካስ ይኸው ነው ሽልማቱ 

በየዕለቱ መሮጡ ጦሙን ማደሩ ሳያንሰው
አሁንም ተማሪ ነው አባ  ትምህርቱን መች ጨረሰው
ሲሞት ብቻ ነው አሱ የነፍሴ እረኛ የሚያርፈው
ላይከብርበት በሥጋው ምንም ነገር ላይተርፈው
ይኸው ዛሬም አይታክትም
የሰው ውሻ ሲጮህበት የምላስ ጅራፍ ሲገርፈው

ሰሙ በሜዳ ይዘራል ያለበደሉ ይከሰሳል
እያገለገለ ይወቀሳል
እንደ ውሃ ፍልቶ ይበርዳል ሳይውድ በግድ ይታገሳል
እንደ ሻማ እየቀለጠ የጥበብ ብርሃኑን ይለግሳል
እያለቀሰ ያስለቅሳል ቁስለኞችን ይፈውሳል

አቅሜ ባይፈቅድልኝም አንኳን ምንም ባላግዘው በጥቂቱ
ከቤተ ክርስቲያን ጓሮ ቆሜ በየዕለቱ
እጸልይለታለሁ እኔ እናቱ

እሱም ቢሆን ጠንካራ ነው እጅግ በጣም የሚያኮራ
የክህነት አገልግሎት ምንም ሲሆንበት መራራ
የመምህሩን ቃል ኪዳን የፈጣሪውን አደራ
ሸክም ሲብደው አንድ ቀን ይጥለዋል ብየ ስፈራ
ሊጥለው አይፈልግም ይነገዳገዳል ያለአቅሙ
ለካስ ለክብር ነው እርሱ የግፍ ቀንበር መሸከሙ

ይህን እያወቅሁ እኔ ለቆመለኝ ለነፍስ አባቴ
ላግዘው ሲገባኝ በጸሎቴ
ክፉ ብናገር ስለእርሱ ትከሰኝ አለች ነፍሴ
ሞት እንደሆን አይቀርም ነገ ይታሠራል ምላሴ  

ጠንቃቃ ሐኪም ነው ብልህ ዳኛ
የማይታክት የማይተኛ
የገነት ቁልፍ በእጁ ያለ የመንገሥተ ሰማያት በረኛ
አባ የነፍሴ እረኛ