HOME FOR SPIRITUAL MESSAGE BY FR ZEMENE DESTA

ቃል ኪዳን እንግባ

ሰው በስደት ሲኖር ከሀገሩ ርቆ
የሀገሩ ወኪል እንደሆነ አውቆ
ለሚሠራው ሥራ በጣም ተጠንቅቆ
የሃይማኖቱን ሕግ እንደ ዝናር ታጥቆ
የዜግነት ክብሩን ባሕሉን ጠብቆ
ልጅ ለአባቱ ታዞ እንደ ልጅነቱ
ሽማግሌው ታፍሮ በአረጋዊነቱ
ተከባብሮ መኖር ሁሉም እንደ እምነቱ
ይህ ነው የጭዋ ደንብ ወግና ሥርጫቱ

የእምነት ማዕከላችን ያለች የነበረች
እንከን የሌላት ወርቅ ከአልማዝ የከበረች
ዜጎች በጭንቅ ቀን የሚጠለሉባት
እኛው ራሳችን  ብንሆንባት ጠላት
እርሷን መራቅ ጤና ተብሎ ስም ወጣላት

ቢዝነስ ተኮር ስብከት በውል የተጠና
የመድረክ እሽቅድድም ለታይታ ለዝና
ለሰላም ካልበጀ ለሕዝቦች አንድነት
ቂም በቀል ያዘለ ሥርዓተ አምልኮት
የዝማሬ ብዛት የማህሌት ድምቀት
ኪሳራ ነው ትርፉ የድካሙ ውጤት

ሳይገባን ምሥጢሩ የሃይማኖታችን
በልማድ ሆነና መሰባሰባችን
ተመቸው ዘንድሮ ሰይጣን ጠላታችን
መቅድስ ዘልቆ ገባ መዘነው ልባችን

ዜጋ ስሙ ገኖ የሚጠራው በዓለም
በበጎነት እንጅ በሁከት አይደለም
በስደትም ስንኖር  ከሀገር ርቀን
ይበጀናል መኖር  ስማችን ጠብቀን
አንቀርም በስደት በሰው አገር ወድቀን
እንመለሳለን  ሁላችን አንድ ቀን
ባለታሪኮች ነን ዓለም ያደነቀን

ቃል ኪዳን እንግባ...፤
በዘር መለያየት ሊቀር አሉባልታ
ለዜግነታችን ልንሰጠው ቦታ
ቃል ኪዳን እንግባ ልባችን ይረታ
ኢትዮጵያውያን ሁሉ እንደ ባሕላችን
ተከባብረን ልንኖር በአንድነት ሁላችን
የምንገናኝባት የእምነት ማዕከላችን
ትንሽዋ ኢትዮጵያ ልትሆን የጋራችን
ታሪክ ተለውጦ  ሊታደስ ስማችን
ቃል ኪዳን እንግባ እኛው ለራሳችን

ቀሲስ ዘመነ አቡሐይ
ሳን ሆዜ ካሊፎርንያ